ከነብዩ (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ውጭ ሙሉ ንግግሩን የምንቀበልለትም ይሁን መሪ ተደርጎ፤ ሚዛን ሊደረግ የሚገባው አንድም ሰው የለም፡፡
=============================
ሸይኽ በክር ኢብን አብደላህ አቡ ዘይድ ‹‹ሁክሙል ኢንቲማ ኢላ ፊርቃ ወል አህዛብ ወል ጀመዓት አል ኢስላሚያ›› በተሰኘው ኪታባቸው ላይ ገፅ 96-97
‹‹ለኡማው አንድን ግለሰብ እንደ መሪ ተደርጎ ሊቀመጥ እና ሰዎች ወደ እርሱ መንገድ ሊጠሩ፤ ወዳጅነትም ጠላትነትም (ለዛ ሰው) ለእርሱ ሲባል ሊፈፀም አይገባም፤ ለእኛ ነብይ እና ለአላህ መልክተኛ ሙሃመድ (ﷺ) ሲቀር፡፡ ከአላህ መልክተኛ ውጭ ያለን በዚህ መንገድ ያስቀመጠ ሰው መንገድ የሳት እና ሙብተዲ (ቢድዓ አራማጅ) ነው፡፡››
ሸይኽል ኢስላም ኢብን ተይሚያ (አላህ ይዘንለት) ‹‹መጅሙኡል ፈትዋ (20/164)›› ላይ እንዲህ ይላል ‹‹አንድን ሰው ለኡማው መርጦ፤ ወደ እርሱ መንገድ መጥራት ሰዎችን በእርሱ ወዳጅ እና ጠላት ማድረግ አይገባም፤ ነብዩን (ﷺ) ሲቀር፡፡
አንድን ንግግርም አስቀምጦ፤ በዛ ንግግር ወዳጅ እና ጠላትን ማድረግ አይቻልም፤ ከነብዩ (ﷺ) ንግግር ውጭ እና ኡማው ኢጅማእ ካደረገበት ውጭ፡፡
ይህ የቢድዐ ሰዎች ተግባር ነው፤ አንድን ሰው እና ለራሳቸው ንግግርን አስቀምጠው፤ ኡማውን የሚበታትኑበት፡፡ ሰውንም በዚህ (እነሱ ባስቀመጡት) ንግግር (ይቀበላል ወይንስ አይቀበልም ብለው)ወዳጅነትን እና ጠላትነትን ያፈርዳሉ››፡፡
ትንሽ ማብራሪያ
=============
አላህ ተከተሉት፤ ታዘዙት፤ አርአያችሁ ነው፤ ተምሳሌታችሁ ነው፤ እኔን መውደዳችሁ ማረጋገጫው እሱን መከተላችሁ ነው፤ ያለው ነብዩ (ﷺ) ብቻ ነው፡፡
ይህ ሆኖ ሳለ፤ ዛሬ ዛሬ ገና አላህ ዘንድ ምን ይሁን ደረጃቸው የማይታወቅ ሰዎች ለኡማው መሪ ተደርገው ተይዘው ‹‹እገሌን ትቀበላለህ ወይንስ አትቀበልም››፤ ‹‹ይህን ተግባር ትቀበላለህ ወይንስ አትቀበልም››፤ ‹‹እነ እገሌ ያሉትን በል፤ ያልተቀበሉትን አትቀበል፤ የተቀበሉትን ተቀበል፤ ዝም ሲሉ ዝም በል፤ ሲናገሩ ተናገር ›› እየተባለ የጥመት እና የቢድዐ አካሄድ አለማችን ላይ በመሰራጨት ይገኛል፡፡ ሌላው የጥመት አባባል ‹‹እገሌ ከእነ ኡስታዝ እንትና ጋር አብሮ አይሰራም›› የሚባል የቡድንተኝነት ወይንም የሂዝብያ መንገድ የሰለፎች መንገድ አይደለም፡፡ ታድያ ከእኛ የሚጠበቀው አንዱን የነብያት ሁሉ ኢማም የሆኑትን ነብይ ቃል መከተል ብቻ ነው፡፡ ሰዎችንም ወዳጅ እና ጠላት ብለን ለመፈረጅ የነብዩን ቃል ይቀበላሉ ወይንስ አይቀበሉም እንጂ ማለት ያለብን፤ ‹‹እገሌን›› ካልተቀበልክ የሚለውን የተሳሳተ አካሄድ እንራቀው፡፡ ሃቅን ከፈለግን፡፡
የአላህ መልክተኛን (ﷺ) ብቻ እንጂ መሪ ማድረግ የሚቻለው፤ ሰዎችን መውደድም ሆነ መጥላት የሚቻለው፤ የነብዩን ንግግር ይቀበላል ወይንስ አይቀበልም ተብሎ እንጂ የሌላ ከእርሳቸው ውጭ ያለን ሰው ማንም ይሁን ማን እንዲህ አድርጎ ደረጃ መስጠት አይቻልም፡፡
ከ Sadat Kemal Abu Nuh የተወሰደ።

No comments:
Post a Comment